Tuesday, October 2, 2012

መስቀል ኃይላችን ነው

መስከረም 16 ቀን እስከ 25 ድረስ ያሉት ቀናት መስቀል የሚል ስያሜ ተሰጥቷቸዋል። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ «የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ነው ለእኛ ለምናምን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነው»1ኛ ቆሮ 1፥18 ብሏል። ይህ መልእክት በተላለፈበት ዘመን ይኖሩ የነበሩት የአብርሃም ዘሮች ነን የሚሉ አይሁድና ለሥጋዊ ጥበብ ከፍተኛ ቦታ ይሰጡ የነበሩ ግሪኮች የክርስትናን እምነት በራሳቸው አመለካከት ለመረዳት የሚሹ ነበሩ። የክርስቶስን የማዳን ጥበብ ለመረዳት አይሁድ በአይናቸው ተአምራትን ለማየት ሲሹ የጥበብ ሰዎች ነን የሚሉት በሥጋዊ ጥበብ የመስቀሉን ቃል ሊመራመሩ ፈልገዋል። ይህ ምስጢር ግን የሚገለጠው በእምነት ለሚፈልጉት ስለሆነ የመስቀሉ የማዳን ሥራ  ከእነርሱ ሊሰወር ችሏል።